Sunday, September 7, 2014

breaking news] የለገጣፎ ነዋሪዎች በ10 ቀን ውስጥ ቤታቸውን እንዲያፈርሱ ታዘዙ




 

• ‹‹ገንዘብ እየጠየቁ ከማስቸገራቸው ውጭ እንድናፈርስ ጠይቀውን አያውቁም››
• ‹‹የሚመጣውን ሁሉ፤ ሞትም ቢሆን ለመቀበል ዝግጁ ነን›› ነዋሪዎቹ
ለገጣፎ ውስጥ በሶስት ጎጦች የሚኖሩ ዜጎች በ10 ቀን ውስጥ ቤታቸውን አፍርሰው እንዲለቁ ትዕዛዝ እንደተላለፈላቸው ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ ጎራጎጭ፣ ዳሌና ድሬ በተባሉት ሶስት ጎጦች እስከ 23 ሺህ ህዝብ ይኖርባቸዋል ያሉት ነዋሪዎቹ በእነዚህ ጎጦች ከ1997 ዓ.ም ጀምረው መኖር እንደጀመሩ ገልጸዋል፡፡

 
ነዋዎቹ የሰንዳፋ ወረዳ ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ጽ/ቤት ማህተም አስቀርጾ የመረዳጃ እድር ማቋቋሙን፣ ለመብራት ኃይል አንድ ሚሊዮን ያህል ገንዘብ ከፍለው ትራንስፎርመር ለማስተከል እየተጠባበቁ መሆናቸውንና፣ የውሃና ሌሎች ተቋማት ህጋዊ ለሆነ አካል የሚሰጡትን አገልግሎት ከፍለው እያገኙ እንደቆዩ በመግለጽ የሚኖሩበት አካባቢ ህገ ወጥ አለመሆኑን አስረድተዋል፡፡

ይሁንና ነሃሴ 26 ተጻፈ የተባለና ከፊንፊኔ ልዩ ዙሪያ በረህ ወረዳ የመሬት አስተዳደር ጽ/ቤት እንደሆነ የሚገልጽ ነገር ግን የመስሪያ ቤቱን ስም፣ ከማህተምና ቀን ውጭ የመዝገብ ቤት ቁጥር፣ ቲተር፣ ፊርማ የሌለው ደብዳቤ ድንገት ትናንት ነሃሴ 30 በመኪና መጥተው ለጥፈው መሄዳቸውን ነዋሪዎቹ ገልጸዋል፡፡
የተለጠፈው ደብዳቤውም ‹‹በዚህ ቦታ የሰፈራችሁ ሰዎች ቦታው የእርሻ ቦታ ስለሆነ ቤታችሁን አፍርሳችሁ እንድትለቁ፡፡ ይህን ካላደረጋችሁ አፍርሽ ግብረሃይል ልከን አስፈርሰን መሬቱን ወደ መሬት ባንክ እንዲገባ እናደርጋለን ›› የሚል መሆኑን የሚገልጹት ነዋሪዎቹ ‹‹የመዝገብ ቤት ቁጥር፣ ቲተር፣ ፊርማ የሌለው ደብዳቤ ለጥፈው በመሄዳቸው እኛ ለማን አቤት እንደምንል ግራ ገብቶናል፡፡ ተጠያቂ የሆነ አካል ማን እንደሆነ እንኳን ለማወቅ ይከብዳል፡፡›› ብለዋል፡፡
ነዋሪዎቹ ጨምረውም ‹‹እስካሁን እንድናፈርስ ተጠይቀን አናውቅም፡፡ ከአሁን ቀደም የነበረብን ችግር ከላይ እስከታች ያሉት አካላት ገንዘብ የሚጥይቁ መሆናቸው ነው፡፡ የተበላሸ አሰራራቸው ነበር የሚያስቸግረን፡፡ የቀበሌ ታጣቂ፣ ፖሊስ ሌሎችም መጥተው ገንዘብ ይጠይቁናል፡፡ አጥር አጠራችሁ ብለው ገንዘብ ይጠይቁናል፡፡ ካልሰጠናቸው እቃችን ሳይቀር ጭነው ይሄዳሉ፡፡ ከዚህ ውጭ ግን እንድንለቅ ጠይቀውን አያውቁም፡፡›› ሲሉ ገልጸዋል፡፡
‹‹በተለጠፈላችሁ ደብዳቤ መሰረት ልታፈርሱ ነው? ምን ልታደርጉ አስባችኋል?›› ብለን የጠየቅናቸው የአካባቢው ነዋሪዎች ‹‹እኛ እያፈረስን አይደለም፡፡ ህዝቡ ጭንቀት ውስጥ ነው፡፡ አፍርሰን የምንሄድበት ቦታ የለንም፡፡ እኛ ልናደርገው የምንችለው የሚመጣውን ነገር ሁሉ፤ ሞትም ቢሆን ለመቀበል ዝግጁ ነን፡፡›› ሲሉ ለነገረ ኢትዮጵያ ገልጸዋል፡፡ በሌላ በኩል የአካባቢው አባ ገዳ አባገዳ ስለሽ ቤታቸውን በ10 ቀን ውስጥ አፍሰው እንዲለቁ ደብዳቤ በመለጠፉ የተረበሹትን የአካባቢውን ነዋሪዎች በማረጋጋት ላይ መሆናቸውን ነዋሪዎቹ ገልጸዋል፡፡
ምንጭ ነገረ ኢትዮጵያ

No comments:

Post a Comment